Skip to main content

የ 2013 የዓለም የሰብአዊ መብቶች ሁኔታ ሪፖርት፡- ኢትዮጵያ

የ 2012 ዋና ዋና ሁነቶች

ኢትዮጵያን ለረጅም ዓመታት በጠቅላይ ሚኒስትርነት የመሩትና ሰፊ ስልጣን የነበራቸው መለስ ዜናዊ በነሃሴ ወር በድንገት መሞት በሃገር ውስጥም ሆነ በኢትዮጵያ ዓለማቀፍ አጋሮች ዘንድ የሀገሪቱን ፖለቲካዊ ሽግግር የሚመለከቱ ጥያቄዎችንና አጠራጣሪ ሁኔታዎችን አስነስቶ ነበር።በኢትዮጵያ ያለው የሰብአዊ መብቶች አያያዝ በተለይ ካለፉት ጥቂት ዓመታት ወዲህ እየከፋ ሄዷል።አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ በመስከረም ወር ስልጣኑን የተረከቡ ቢሆንም መንግስት በርሳቸው አመራር ሰብአዊ መብቶችን የሚመለከቱ ለውጦች ያደርግ ወይስ አያደርግ እንደሆነ ገና የሚታይ ነው።

እ.ኤ.አ በ2012ም የኢትዮጵያ ባለስልጣናት መሰረታዊ የሆኑትን ሃሳብን በነጻ የመግለጽ፣ የመደራጀት እና የመሰብሰብ መብቶች በጥብቅ መገደባቸውን ቀጥለዋል።ለኣሻሚ ትርጉሞች በተጋለጠውና በ2002 ዓ.ም በወጣው የሀገሪቱ የጸረ ሽብርተኝነት ሕግ 30 ጋዜጠኞችና የተቃዋሚ ፖለቲካ ፓርቲ አባላት ተከሰው ተፈርዶባቸዋል።በዋና ከተማዪቱ አዲስ አበባ እና በኦሮሚያ ክልል የእስልምና እምነት ተከታዮች ላካሄዷቸው የተቃውሞ ሰልፎች የጸጥታ ሃይሎች የሰጡት ምላሽ የዘፈቀደ አፈሳ፣ እስር እና ድብደባ ነበር።

የኢትዮጵያ መንግስት በአምስት ክልሎች የሚኖሩ የገጠር ነዋሪዎችን የተሻለ የመሰረታዊ ግልጋሎቶች አቅርቦት ሊያገኙ ወደሚችሉባቸው አካባቢዎች ለመውሰድ በሚል ምክንያት 1.5 ሚሊዮን የገጠር ነዋሪዎችን መልሶ ለማስፈር የሚያካሂደውን የሰፈራ ፕሮግራም ቀጥሎበታል።በጋምቤላ ክልል የሚገኙ በርካታ ነዋሪዎች ከፍላጎታቸው ውጭ በሃይል እንዲፈናቀሉ በመደረጋቸው ለከፍተኛ ችግሮች ተጋልጠዋል። ከዚህ በተጨማሪም መንግስት ለሚያካሂደው ሰፊ የስኳር ልማት መሬት ለማስለቀቅ ሲባል በኢትዮጵያ የታችኛው ኦሞ ሸለቆ ነዋሪ የሆኑትን አርብቶ አደር ማህበረሰቦች ከመኖሪያቸው እንዲፈናቀሉ እያደረገ ነው።

ሃሳብን በነጻ የመግለጽ፣የመደራጀት እና የመሰብሰብ መብቶች

መንግስታዊ ያልሆኑ ደርጅቶችን እንቅስቃሴ ለመቆጣጠር  የበጎ አድራጎት ደርጅቶች እና ማህበራት አዋጅ እንዲሁም የጸረ ሽብርተኝነት ሕግ በ2002 ዓ.ም ከታወጁ ወዲህ በኢትዮጵያ ሃሳብን በነጻ የመግለጽ፣የመሰብሰብ እና የመደራጀት መብቶች ከፍተኛ ገደብ ተጥሎባቸዋል። እነዚህ ሁለት ሕጎች መንግስት በሲቪል ማህበረሰብ መሪዎች፣በጋዜጠኞች እና በሌሎችም የመንግስትን ፖሊሲ በሚተቹና መንግስት እንዲነሱ በማይፈልጋቸው ጉዳዮች ላይ ሃሳባቸውን በሚገልጹ ሰዎች ላይ ካካሄደው ሰፊ እና የማያቋርጥ ማዋከብ፣ዛቻ እና ማስፈራራት ጋር ተዳምሮ ያስከተሉት  ውጤት የከፋ ነው።

ኢትዮጵያ ውስጥ እጅግ የጎላ እንቅስቃሴ ያደርጉ የነበሩ የሰብአዊ መብቶች ድርጅቶች እንቅስቃሴዎቻቸውን በከፍተኛ ሁኔታ እንዲቀንሱ ወይም ሰብአዊ መብቶችን የሚመለከቱ ጉዳዮችን ከስራ ዝርዝራቸው ውስጥ እንዲያወጡ የተገደዱ ሲሆን ቁጥራቸው ያልታወቀ ድርጅቶችም ጭራሹኑ ተዘግተዋል። በደረሰባቸው ማስፈራሪያ ምክንያት ሰፊ ልምድና መልካም ስም የነበራቸው ብዙ የሰብአዊ መብቶች ተሟጋቾች ሃገሪቱን ለቀው ሄደዋል። አሁን ሰፍኖ የሚገኘው ሁኔታ ለነጻ ፕሬስ እንቅስቃሴም እንዲሁ የተመቸ አይደለም።ባለፉት አስር ዓመታት በደረሰባቸው ዛቻ እና ማስፈራራት ሳቢያ ሃገራቸውን ለመልቀቅ በተገደዱ ጋዜጠኞች ቁጥር በዓለም ኢትዮጵያ ቀዳሚዋ ናት። የጋዜጠኞች መብት ተሟጋች የሆነው ድርጅት ሲፒጄ እንደሚገልጸው ቢያንስ 79 ጋዜጠኞች ሃገራቸውን ለቀው ለመሰደድ ተገደዋል።

የጸረ ሽብርተኝነት አዋጁ፣ ተቃዋሚ ናቸው ተብለው የሚታሰቡ ሰዎችን ዒላማ ለማድረግ፣ተቃውሞን ለማፈን እና ጋዜጠኞችን ዝም ለማሰኘት ስራ ላይ እየዋለ ነው። እ.ኤ.አ በ2012 ዓ.ም 30 የፖለቲካ መሪዎች፣ የተቃዋሚ ፓርቲ አባላት እንዲሁም ጋዜጠኞች በግልጽ ባልተብራሩ የሽብርተኝነት ወንጀሎች ተከሰው ተፈርዶባቸዋል።ከ2011 ጀምሮ ባለው ጊዜ ውስጥ 11 ጋዜጠኞች በዚሁ ሕግ ተከሰው ተፈርዶባቸዋል።

ጥር 17 ቀን 2004 ዓ.ም አሁን የተዘጋው አውራምባ ታይምስ ጋዜጣ ምክትል አዘጋጅ በነበረው ውብሸት ታዬ እና የጋዜጣው ዓምደኛ በነበረችው ርዕዮት ዓለሙ ላይ በአዲስ አበባ የሚገኝ ፍርድ ቤት የ 14 ዓመታት እስር ፈርዶባቸዋል።የርዕዮት ዓለሙ ፍርድ በኋላ በይግባኝ ወደ አምስት ዓመታት የተቀነሰ ሲሆን ከቀረቡባት ክሶች ውስጥም አብዛኞቹ ተሰርዘዋል።

ከፍተኛ ክብር ያለውን የፔን አሜሪካ ፍሪደም ቱ ራይት ሽልማት በሚያዝያ ወር 2004 ዓ.ም ያሸነፈው አንጋፋው ጋዜጠኛ እና ብሎገር እስክንድር ነጋ ሐምሌ 6 ቀን 2004 ዓ.ም ከሌሎች ጋዜጠኞችና የተቃዋሚ ፓርቲ አባላት ጋር በቀረበበት ክስ የ 18 ዓመታት እስራት ተፈርዶበታል። በስደት ላይ የሚገኙት ጋዜጠኞች አብይ ተክለማርያም እና መስፍን ነጋሽም እስካሁን ድረስ ጋዜጠኞች ላይ ብቻ ተግባራዊ በተደረገው የጸረ ሽብርተኝነት ሕጉ አንቀጽ መሰረት ጥፋተኛ ተብለው እያንዳንዳቸው የ 8 ዓመታት እስራት ተፈርዶባቸዋል። በይፋ ተመዝግቦ የሚንቀሳቀሰው ተቃዋሚ ፓርቲ አንድነት ለፍትሕ እና ለዲሞክራሲ አባል የሆነው አንዷለም አራጌ በስለላ፣ሕገ መንግስታዊ ስርዓቱን በመናድ እንዲሁም የሽብር ተግባር ለመፈጸም ምልመላ እና ስልጠና በማካሄድ ወንጀሎች ጥፋተኛ ተብሎ የዕድሜ ልክ እስራት ተፈርዶበታል።

በመስከረም ወር 2004 ዓ.ም የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የእስክንድር ነጋ እና በስደት ላይ የሚገኘው ጋዜጠኛ አበበ በለው  እንዲሁም የተቃዋሚ ፖለቲካ ፓርቲ አባሉ አንዷለም አራጌ ንብረቶች እንዲወረሱ ትዕዛዝ ሰጥቷል።

ፍትሕ ጋዜጣ የእስልምና እምነት ተከታዮች የሚያካሂዱትን ተቃውሞ እና የጠቅላይ ሚኒስትሩን የጤንነት ሁኔታ አስመልክቶ ያዘጋጃቸው ዘገባዎች የሃገሪቱን ብሔራዊ ደህንነት አደጋ ላይ የሚጥሉ ናቸው በማለት መንግስት ሀምሌ 20 ቀን ጋዜጣው እንዳይሰራጭ አግዷል። ነሃሴ 18 ቀን 2004 ዓ.ም የፍትሕ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ተመስገን ደሳለኝ በቁጥጥር ስር ውሎ ዋስትና ተከልክሏል። ተመስገን ነሃሴ 24 ቀን ከእስር የተለቀቀ ሲሆን ተጨማሪ ምርመራ እስኪካሄድ ድረስ ሁሉም ክሶች ተነስተውለት ነበር።

ሀምሌ 13 ቀን 2004 ዓ.ም ‘የሙስሊሞች ጉዳይ’ የተሰኘው ተወዳጅ የሙስሊሞች መጽሄት ዋና አዘጋጅ የሆነው የሱፍ ጌታቸው ቤት በፖሊሶች የተፈተሸ ሲሆን በዚያው ዕለት ምሽትም የሱፍ በቁጥጥር ስር ውሏል። መፅሄቱ ከዚያ በኋላ መታተም ያቆመ ሲሆን ይህ ዘገባ እስከሚዘጋጅበት ጊዜም የሱፍ በቁጥጥር ስር ይገኛል።

በሕገ ወጥነት ከተፈረጀው አማጺው የኦጋዴን ብሔራዊ ነፃነት ግንባር ጋር በምስራቃዊ ኢትዮጵያ ሲንቀሳቀሱ በቁጥጥር ስር የዋሉት ማርቲን ሺብዬ እና ዮሃን ፒርሰን የተባሉ ሁለት ስዊድናውያን ጋዜጠኞች ለሽብርተኛ ድርጅት ድጋፍ በመስጠት ወንጀል  ታህሳስ 17 ቀን 2004 ዓ.ም የጥፋተኝነት ውሳኔ ተሰጥቶባቸዋል። በተጨማሪም በሕገ ወጥ መንገድ ወደሃገሪቱ በመግባት ጥፋተኞች ተብለዋል።ፍርድ ቤቱም በ 11 ዓመት እስራት እንዲቀጡ ወስኗል። ሁለቱ ጋዜጠኞች አዲሱን ዓመት በማስመልክት በየዓመቱ ለእስረኞች በሚሰጠው ምህረት ከሌሎች 1950 በላይ ከሚሆኑ እስረኞች ጋር ምህረት ተደርጎላቸው ጳጉሜ 5 ቀን 2004 ዓ.ም ከእስር ተለቀዋል።

መንግስት በሃገሪቱ የእስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ጉዳዮች ምክር ቤት ውስጥ የሚያደርገውን ጣልቃ ገብነት በመቃወም ለታቃውሞ የወጡ የእስልምና እምነት ተከታዮችን ለመበተን በሐምሌ ወር 2004 በተለያዩ ቀናት የፌደራል ፖሊስ ድብደባን ጨምሮ ከልክ ያለፈ ሃይል ተጠቅሟል።ሀምሌ 6 ቀን አዲስ አበባ ወደሚገኘው  የአወሊያ መስጊድ በሃይል በመግባት ፖሊሶች መስኮቶችን የሰባበሩ ሲሆን በመስጊዱ ውስጥ አስለቃሽ ጭስ ተኩሰዋል። ሐምሌ 14ም  በመስጊዱ ለተቃውሞ ተቀምጠው የነበሩ ሰዎችን ሃይል በመጠቀም እንዲበተኑ አድርገዋል። ከሐምሌ 12 እስከ 14 በነበሩት ቀናትም በርካታ ሰዎች የታፈሱ ሲሆን 17 ከፍተኛ የእምነቱ መሪዎች በቁጥጥር ስር ውለው ክስ ሳይመሰረትባቸው ከአንድ ሳምንት በላይ በእስር ቆይተዋል።ብዙዎቹ ታሳሪዎች በእስር ላይ እያሉ ማንገላታት እንደተፈጸመባቸው ገልጸዋል።

ተገዶ መፈናቀል

ሰፈራ በሚባለው ፕሮግራሙ የኢትዮጵያ መንግስት በአምስት ቆላማ ክልሎች ማለትም በጋምቤላ፣ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ፣በአፋር፣ በደቡብ ብሄሮች፣ ብሄረሰቦች እና ሕዝቦች እንዲሁም በሶማሌ ክልሎች የሚኖሩ 1.5 ሚሊዮን የሚደርሱ ሰዎችን የተሻለ የመሰረታዊ አገልግሎቶች አቅርቦት ወደሚያገኙባቸው አካባቢዎች ለማዛወር በሚል ወደሌሎች ቦታዎች ወስዶ ለማስፈር እቅድ አለው።

በጋምቤላ እና በደቡብ ኦሞ ሸለቆ ከነዋሪዎች ጋር በቂ የቅድሚያ ምክክር ሳይደረግ እና የካሳ ክፍያ ሳይፈጸም አስገድዶ የማፈናቀል ተግባር እየተፈጸመ ነው።ሂዩማን ራይትስ ዎች እንዳረጋገጠው በተለይ በጋምቤላ ወደሌሎች አካባቢዎች አዛውሮ የማስፈሩ ሂደት የሚከናወነው ብዙ ጊዜ ነዋሪዎቹን ለም የሆኑ መሬቶቻቸውን በማስለቀቅ አነስ ያለ ለምነት ወዳላቸው መሬቶች በማስፈር ነው።ወደ አዳዲሶቹ መንደሮች እንዲሰፍሩ የሚላኩት ሰፋሪዎች አብዛኛውን ጊዜ መሬታቸውን መመንጠር እና ጎጆዎቻቸውን መስራት ያለባቸው ሲሆን ይህንንም በወታደሮች ተቆጣጣሪነት ያከናውናሉ።ቃል የተገቡላቸው አገልግሎቶች ማለትም ትምህርት ቤቶች፣ክሊኒኮች እና የውሃ ፓምፖች የተሟሉ አይደሉም።

በደቡብ ኦሞ ቁጥራቸው ወደ ሁለት መቶ ሺህ የሚደርስ ተወላጅ ሕዝቦች መንግስት ለሚያካሂደው የስኳር ልማት ቦታ ለማስለቀቅ ሲባል መሬታቸው ተወርሶ ወደሌሎች አካባቢዎች እንዲሰፍሩ እየተደረገ ነው። ነዋሪዎቹ ከመሬቶቻቸው ላይ በሃይል እነደሚነሱ፣የግጦሽ መሬቶቻቸው በጎርፍ እንዲጥለቀለቁ እንደሚደረግ፣ ማሳዎቻቸው እንደሚገለበጡ እንዲሁም ለህልውናቸው እና ለአኗኗር ዘይቤአቸው እጅግ አስፈላጊ የሆነውን የኦሞ ወንዝ ውሃ እንዳያገኙ እንደሚከለከሉ ተናግረዋል።

ሕገ ወጥ ግድያ፣ማሰቃየት እና በቁጥጥር ስር ባሉ ሰዎች ላይ የተፈጸሙ ጥሰቶች

በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል በጋሸሞ ወረዳ ራቅዳ በተባለች መንደር ከነዋሪዎች ጋር የተፈጠረን ግጭት ተከትሎ ‘ልዩ ሃይል’ በሚል ስያሜ የሚታወቅ፣ በኢትዮጵያ መንግስት የሚደገፍ ታጣቂ ቡድን በቁጥጥሩ ስር የነበሩ 10 ሰዎችን እና ሌሎች 9 የመንደሩ ነዋሪዎችን የገደለው መጋቢት 7 እና 8 ቀን 2004 ዓ.ም ነበር።

በሚያዝያ ወር 2004 ዓ.ም ማንነታቸው ያልታወቀ መሳሪያ የታጠቁ ሰዎች በጋምቤላ ክልል በሚገኝ እና ባለቤትነቱ የሳውዲ ስታር ኩባንያ በሆነ ሰፊ እርሻ ላይ ጥቃት ሰንዝረዋል። ይህ የእርሻ ልማት በክልሉ የሰፈራ ሂደት በተካሄደበት ወቅት የከፋ የመብቶች ጥሰቶችና ማንገላታት ከተፈጸመባቸው አካባቢዎች በቅርብ ርቀት ላይ የሚገኝ ነው። ለዚህ ጥቃት ምላሽ ለመስጠት የኢትዮጵያ ወታደሮች ቤት ለቤት በመዞር ድርጊቱን ፈጽመዋል ተብለው የተጠረጠሩ ሰዎችን የፈለጉ ሲሆን የአካባቢውን ነዋሪዎችም ‘አማጺያኑ’ የሚገኙበትን ቦታ አጋልጡ በማለት ሲያስፈራሯቸው ነበር። ወታደሮቹ በርካታ ወጣት ወንዶችን በዘፈቀደ ከማሰራቸውም በላይ ስለ ጥቃቱ መረጃ ለማግኘት ባደረጉት ሙከራ ማሰቃየት፣አስገድዶ መድፈር እንዲሁም ሌሎች ጥሰቶችን በብዙ ነዋሪዎች ላይ ፈጽመዋል።

ሂዩማን ራይትስ ዎች በአዲስ አበባ ማዕከላዊ በመባል በሚታወቀው የፌደራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ጣቢያ እና በክልሎች በሚገኙ የእስር ቦታዎች እንደዚሁም በሶማሌ፣ በኦሮሚያ እና በጋምቤላ ክልሎች በሚገኙ ወታደራዊ ካምፖች ውስጥ የሚፈጸሙ የማሰቃየት ድርጊቶችን የሚመለከቱ መረጃዎችን ማሰባሰቡን ቀጥሏል። በእነዚህ የእስር ጣቢያዎች ከፖለቲካ ጋር በተያያዙ ጉዳዮች የተያዙ ታሳሪዎች ከጠበቆቻቸው ጋር የሚገናኙበት እድል በጣም የመነመነ ሲሆን በቁጥጥር ስር የዋሉ ሰዎች ከፍርድ ሂደት በፊት እና በፍርድ ሂደት ወቅት ሊከበሩላቸው የሚገቡ መብቶችን ለማክበር ያለው ፍላጎትም  በጣም አናሳ ነው። ይህም ታሳሪዎቹን ለከፉ ጥሰቶች ያጋልጣቸዋል።

የስደተኛ ኢትዮጵያውያን የቤት ሰራተኞች አያያዝ

በሊባኖስ የቤት ሰራተኛ የነበረቸው ኢትዮጵያዊት ዓለም ደቻሳ ደሲሳ ድብደባ ሲፈጸምባት የሚያሳየው ቪዲዮ ከተሰራጨና ይህነኑ ተከትሎም ዓለም መጋቢት 5 ቀን 2004 ዓ.ም ሕይቷን ካጠፋች በኋላ በአስር ሺዎች የሚቆጠሩት በመካከለኛው ምስራቅ ሃገራት በቤት ሰራተኝነት የሚሰሩ ኢትዮጵያውያን ሴቶች የሚደርስባቸው መከራ የተጠናከረ ትኩረት አግኝቶ ነበር። ብዙ በስደት የሚሰሩ የቤት ሰራተኞች ወደ ውጭ ሃገራት ሄደው ከመቀጠራቸው በፊት ከባድ የገንዘብ ዕዳ ውስጥ ይገባሉ፤ እንዲሁም ከቅጥር ሂደቱ ጋር የተያያዙ ሌሎች ማንገላታቶች ይፈጸሙባቸዋል።ውጭ ሀገር ሄደው ስራ ከጀመሩም በኋላ ለረጅም ሰዓታት ከመስራት በተጨማሪ ባርነት በሚመስሉ የስራ ሁኔታዎች ውስጥ እንዲሰሩ ይደረጋሉ፣ እንዲሁም ሌሎች  መጠነ ሰፊ ጥቃቶች ይደርሱባቸዋል።(የተባበሩት አረብ ኤሚሬቶች፣ሳኡዲ አረቢያ እና ሊባኖስን የሚመለከቱትን ምዕራፎች ይመልከቱ)።

ዋና ዋና ዓለማቀፍ አጋሮች

በመለስ ዜናዊ አመራር ኢትዮጵያ በአካባቢ ጉዳዮች ላይ የጎላ ሚና ትጫወት ነበር።ወደ አወዛጋቢው የሱዳን አቢዬ ክልል በተባበሩት መንግስታት ስር የሰላም አስከባሪ ሃይሎችን አሰማርታለች፣በሱዳን እና በደቡብ ሱዳን መካከል የነበረውን አለመግባባት ሸምግላለች እንዲሁም አል ሸባብን ለመውጋት የተደረገውን ዓለማቀፍ ጥረት ለማገዝ ሰራዊቷን ወደሶማሊያ ልካለች። እ.ኤ.አ ከ 1998-2000 ድረስ በሁለቱ ሀገራት መካከል የተካሄደውን ከፍተኛ ዋጋ ያስከፈለ ጦርነት ተከትሎ ኢትዮጵያ ከጎረቤቷ ኤርትራ ጋር ያላት ግንኙነት መልካም አይደለም። ኤርትራ ለግጭቱ መነሻ የነበሩ ቦታዎች ለኤርትራ እንደሚገቡ የወሰነውን የድንበር ኮሚሽን ውሳኔ የተቀበለች ሲሆን  ኢትዮጵያ ግን ውሳኔውን አልተቀበለችም።

ኢትዮጵያ ለምዕራብ መንግስታት ጠቃሚ ስትራተጂያዊና የደህንነት አጋር ስትሆን ከእነዚህ መንግስታት በአፍሪካ ከፍተኛውን የልማት እርዳታ የምታገኝ ሀገርም ናት።በአሁኑ ወቅት ኢትዮጵያ በዓመት  ወደ 3.5 ሚሊዮን የሚደርስ የአሜሪካን ዶላር በረጅም ጊዜ የልማት እርዳታ መልክ ታገኛለች።የለጋሽ ሃገራት ፖሊሲዎች በሀገሪቱ እየከፋ ከሄደው የሰብአዊ መብቶች ሁኔታ ጋር በተያያዘ ብዙም የተለወጡ አይመስሉም።

እ.ኤ.አ በመስከረም ወር 2012 የዓለም ባንክ ራሱ እና ሌሎችም የልማት ተቋማት ዘለቄታ ላለው ልማት እጅግ አስፈላጊ ናቸው የሚሏቸውን የሰብአዊ መብቶች እና የመልካም አስተዳደር መርሆች ብዙም ከግምት ውስጥ ያላስገባ አዲስ ብሔራዊ የጋራ ሰትራተጂ ባንኩ አጽድቋል።ባንኩ በተጨማሪም ሦስተኛውን ዙር የመሰረታዊ አገልግሎቶች ጥበቃ ፕሮግራም (ፒቢኤስ 3)ያለፈቃድ የሚደረግ ሰፈራን የሚከለክሉ እና ለተወላጅ ሕዝቦች ጥበቃዎችን የሚያደርጉ ድንጋጌዎችን ሳያካትት አጽድቋል።